
ወቅቱ በግራ-ዘመም ህልዮት የሚበየን አብዮት፣ የችግሮች ሁሉ መፍቻ “ቁልፍ” ተደርጎ እንደ ሃይማኖት የታመነበት ነበር። የ“ያ ትውልድ” መንፈስም፣ በዚሁ እሳቤ ይጠመቅ ዘንዳ ያ ዘመን አስገዳጅ ሆነ። የእዚህ ግፊት ደግሞ፣ ባልጠራ ርዮተ- ዓለም እና በሃሳዊያን ግርግር ሲዋከቡ የሰነበቱትን አዛውንት ንጉሠ-ነገሥት ከዙፋናቸው አፈናቀለ። አራት ኪሎም ከብሔር-የለሹ የአገሪቱ ጦር ሠራዊት በተውጣጡ የበታች መኮንኖችና ወታደሮች መዳፍ ውሎ-ማደሩን ተላመደ። በርግጥ፣ የ“ኮሚቴው” አመራር በጥቂት ዐመታት ውስጥ ተበትኖ፣ ደመ-ቁጡው ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምን ብቸኛው “ጠንካራ-ሰው” ከመሆን ያገዳቸው አልነበረም። በሂደትም፣ የለውጡ ባቡር ከ“ኢትዮጵያ ትቅደም!” ወደ “ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር!” ዞረ።
በሰንሰለታማው የትግራይ ተራራ ስር ደግሞ ዐዲስ የታሪክ ምዕራፍ እየተገለጠ ስለመሆኑ ያስተዋለው አልነበረም። ለራሳቸው “ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ” የሚል ስያሜ የሰጡት የዐድዋ-አክሱም ጎረምሶች፣ በትጥቅም ሆነ ስንቅ እየደረጁ ነው። የቡድኑ ፈጣሪዎች የሸፈቱለትን “የትግራይ ሪፐብሊክ” የማወለድ አጀንዳቸውን ከከለሱ በኋላ ደግሞ፤ በተለያዩ ሚደያዎችና በፕሮፓጋንዳ ማሽኖቻቸው፣ ዓላማቸው የደርግ ሥርዐትን መገርሰስ እና የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ነፃ ወጥተው፣ በእኩልነት የሚተዳደሩበት ሥርዐት ማንበር እንደሆነ በዐማርኛ እና እንግሊዘኛ አብዝተው አስተጋብተዋል። ምንም እንኳ በትግርኛ፣ ዐማራን በተለይ፣ ሸዋን “ጠላት” ብለው ቢፈርጁም ቅሉ።
ነገሮች እንዲህ በተወሳሰቡበት ወቅት ነው፣ አንድ የሕወሓት “ሰው” በቁጥጥር ስር የዋለው። ይህን ተከትሎም፣ ታላቅ ምስጢር አድርገው የያዙት ድብቁ ዓላማቸው እና የትግል ጽሑፎቻቸውን የተመለከቱ ማስረጃዎች በደህንነቱ መስሪያ ቤት ጠረጴዛ ተከመሩ። በጊዜው በሚኒስትሮች ምክር ቤት የኢኮኖሚ እና ማኀበራዊ ዘርፍ ኃላፊ የነበሩት ጓድ ፋሲካ ሲደልል ከሕወሓቱ ሰውዬ የተገኙት መረጃዎች፡-
“የትግራይ ጥላቶች ማናቸው? አንደኛ ዐማራ። […] ሥልጣኑን ከዐፄ ዮሃንስ ላይ ነጥቀዋል። […] ሁለተኛ ኦሮሞ፣ ከዐማራ ጋር እየሆነ እየወጋን ነው። ሦስተኛ ጉራጌ፤” ብለው መደምደማቸውን የሚያረጋግጡ እንደነበረ ባለፈው ሳምንት ለ“ዐማራ ሚደያ ኮርፕሬሽን” አብራርተዋል።
Be the first to comment