
መንግሥትን ለመፈንገል ከተሞከረው ሰሞነኛው አደገኛ ሴራ ጀርባ፣ የማን እጅ እንዳለ ለኢትዮጵያ ሕዝብ መንገሩ ለቀባሪው ማርዳት ነው። እቅዱ ገና ከጅምሩ ከሸፈ እንጂ፤ የአሜሪካው ማዕከላዊ የስለላ ተቋም CIA፣ በሌሎች አገራት ሞክሮ ካሳካው መንግሥት የመፈንቀል ሴራ ጋር በብዙ ይመሳሰላል።
በርግጥም፣ ከላንግሌይ እስከ ናይሮቢ የነበረውን እንቅስቃሴ የተከታተለ ሰው ችግሩን ከአናቱ ይይዘዋል። ከእንጦጦው ኤምባሲ እስከ ሮም ስቴሽን ያሉ የአሜሪካ ማዕከላዊ ስለላ ተቋም ወኪሎች ተልዕኮውን በግንባር ቀደምትነት መርተውታል። ለዚህም እማኝ የሚሆነው አንዳንዴ በስውር፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ በዐደባባይ የሚታየው የሴራ ጉንጎና እና ሽረባቸው ነው። በጥቅሉ፣ አገራትን በማተራመስ እና የመንግሥት ግልበጣን በማቀነባበር ከፍተኛ ልምድ ያላቸው ባለሙያዎች ያሳዩት እንቅስቃሴም ሆነ የአሜሪካ እና የአውሮፓ “subversion and regime change experts” ከዝግጅቱ እስከ አፈጻጸሙ የነበራቸው አስተዋጽኦ ለዚህ ምስክር ነው።
የብሪታኒያው MI6፣ የጀርመኑ BND፣ የፈረንሳዩ DGSEን ጨምሮ፤ እስከ ቤልጅየሞቹ VSSG ተወርዋሪ ወኪሎች፣ በሴራው ላይ ተሳትፈዋል። እንደ CNN፣ BBC፣ AFP፣ Routers እና The Economist ያሉ ዋና ዋና የምዕራብ ዜና አውታሮችም እጃቸውን በስፋት አስገብተዋል። በመንግሥት ግልበጣው እቅድ ላይ የሜዲያው ሚና እጅግ ከባድ መሆኑን ለማገንዘብ፣ ሁሉም በአንድ ግዜ የተቀነባበረ የፈጠራ ወሬና የሃሰት መረጃ ማሰራጨታቸውን ማስተዋሉ በቂ ነው። ይህንን እኩይ ሚና ለመወጣት ሲሉም፣ ዓለም ዐቀፉን የሜዲያ መርህ በመጣስ፣ በመልካም ስማቸው ላይ ጥላሸት መቀባት ነበረባቸው።
በዚህ የፍልሚያ ጎራ የተሰለፉት የውጭ መገናኛ ብዙሃን ብቻ አይደሉም። በአገር ውስጥ አምስተኛ ረድፈኞችም በተደራጀ መልኩ ሲሳተፉ ታዝበናል። ቀድሞ የተደራጁ ተከፋዮች ከላይ የተሰጣቸውን ትዕዛዝ ለመፈጸም፦ ባለሥልጣናት፣ ባለሃብቶች፣ አርቲስቶች እና ታዋቂ ግለሰቦች ከአገር እንዲወጡ የሚገፋፋ ሃሰተኛ መረጃዎችን ከማሰራጨት ጀምሮ፣ በአካል እየተገናኙ እስከ ማሸበር የተለጠጠው ድፍረታቸው የሴራው ጉልህ አካል ለመሆኑ ዋንኛ ማሳያ ነው።
Be the first to comment