
መግቢያ፣ ምነው የምዕራቡ ዓለም ሚድያ እብዝቶ ጠመደን!? ያን ሁሉ የሀሰት ዘገባ እና ስም ማጥፋትንስ ምን አመጣው? በዚህ ጽሑፍ እነዚህን ጥያቄዎች እንመልሳለን።
የምዕራባዊያን የአቋም ለውጥ ምክንያት፡–
ታስታውሱ እንደሆን ሕወሓት ተሽሮ፣ በዶ/ር ዐቢይ አህመድ የሚመራው የለውጥ ኃይል ሥልጣን ላይ እንደወጣ፣ አንድ የአሜሪካ ሴናተር ያስተላለፉት መልዕክት “Game over, TPLF” የሚል ነበር። “ሕወሓት አለቀልሽ”። እንደተባለውም፣ ጨዋታው አልቆ ነበር። በአንጻሩ የምዕራቡ ዓለም ድጋፍ ከዐዲሱ አመራር፣ በተለይ ከዶ/ር ዐቢይ ጋር ነበር ለማለት ይቻላል። አልፎ ተርፎም የኖቤል የሰላም ሽልማት ማግኘታቸውም ይታወቃል።
ዛሬ ደግሞ፣ አውሮፓ ሕብረትና አሜሪካ የሕወሐት ደጋፊ ሆነው፣ ጠቅላይ ሚንስትሩን ለመወንጀል ውሸት ፈብራኪ ዘጋቢዎቻቸውን አሰማርተዋል። በሕወሓት ቀስቃሽነት በተነሳው ጦርነትም፣ ዶ/ር ዐቢይ የሚመሩት የኢትዮጵያ ሠራዊት ሲያጠቃ “ተው!”፣ ሲጠቃ “ተደራደሩ?!” ይላሉ።
ግን፣ አሰላለፋቸውን ለምን ቀየሩ? ቢያንስ ሁለት ምክንያቶችን ማንሳት ይቻላል። አንዱ የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር በባይደን መቀየሩ ሳይሆን አይቀርም። ምክንያቱም ትራምፕ አንድ የአገር መሪ ቅድሚያ ለዜጋው መስጠት እንደሚገባው የሚያምኑና የሚሰብኩም ነበሩ። ስለ አፍሪካ ጸያፍ መናገራቸው፣ በግድባችን ላይም በእብሪት መደንፋታቸው ቢታወቅም፤ “ቅድሚያ ለራስ አገር” እና “አሜሪካ ትቅደም!” በሚሉት መፈክር የተገለጸው አቋማቸው ፍትሐዊ ነበር ለማለት ይቻላል።
በአንጻሩ፣ የባይደን አስተዳደር ‹ዓለምን ካላስተዳደርኩ› የሚለውን የቆየ የአሜሪካ አቋም የሚያራምድ መሆኑ ይታወቃል። ምንም እንኳ፣ ዛሬ አሜሪካ ዓለምን ለመምራት የሚያስችል የንድፈ ሐሳብም ሆነ የሞራል የበላይነት ባይኖራትም፤ በጉልበትም ቢሆን በአፍጋኒስታን እንደታየው ተዋርዳ መፈርጠጧ እውነት ቢሆንም፤ የሚፈራላት ካገኘች ግን፣ ከማስፈራራት እንደማትቦዝን ለማየት ይቻላል። የባይደን አስተዳደር ‹አቤት›፣ ‹ወዴት› የሚል ታዛዥ “የድኻ” አገር ባለሥልጣን የሚፈልግ፣ የአገሩንም ዐቅም ለእጅ ጥምዘዛ የሚጠቀም መሆኑ አንዱ ነው።
Be the first to comment