
“ከአጋም የተጠጋ ቁልቋል ሁሌም ሲደማ ይኖራል” እንዲሉ፤ የዋግ ሕዝብ ከትሕነግ መፈጠሪያ ክልል ድንበር በመጠጋቱ፣ ከዘመነ ደርግ ጀምሮ ሲደማ እንዲኖር አድርጎታል። ዛሬም በዚሁ እሾህ እየደማ ነው። በርግጥ፣ ትሕነግ ከሥነ-ፍጥረቱ ጀምሮ ሀሳቡ ጥላቻ፣ ድርጊቱ ግብረ- አጋንንት እንደሆነ ቢታወቅም ቅሉ፤ በዋግ ሕዝብ ላይ የማያባራ መከራና ስቃይን ማዝነብ የጀመረው ደደቢት በረሃን በረገጠ ማግስት ነው። ገና ያኔ በደደቢት ሸለቆዎች በሚሽሎከለክበት ጊዜ፣ ከሰቆጣ ከተማ የሲቪሎችን ሀብትና ንብረት ይዘርፍ ነበር። ከ1970ዎቹ መጨረሻ ዐመታት ጀምሮ ደግሞ፣ በተከታታይ የዋግ አርሶ ዐደርን እንስሳት እና የማሳ ሰብልን አያራቆተ ኖሯል።
የዋግ ሕዝብ በፀረ-ደርግ ትግሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ልጆቹን ገብሮ፣ ትሕነግን ለሥልጣን ቢያበቃውም፤ ለውለታው ያገኘው “ሽልማት” ዋግ ኽምራን ከሁሉም አከባቢዎች በተለየ መልኩ በልማት ወደኋላ ማስቀረትን ነው።
በመስከረም 2013 ዓ.ም የትሕነግ መሪዎች ‹‹የትግል ልዩ ምዕራፍ እድገቶች እና የምከታችን ቀጣይ ስትራቴጂዎች፣ ስልቶች እና አቅጣጫዎች›› በሚል ርዕስ ባዘጋጁት ሰነድ፣ ዋግ የጦርነት መራኮቻ ቦታ (buffer zone) መሆን እንዳለበት በግላጭ አስቀምጠዋል። በእነሱ ስሌት፣ የዋግ መልከዐ-ምድር እና ሕዝብ ወደ ትግራይ ለሚመጣም ሆነ ከትግራይ ለሚነሳ ጦር፣ የጥይት ማብረጃ እንዲሆን ቀድመው ፈርደውበታል። ይህንን እቅዳቸውን ተግብረውትም አሳይተውናል።
ሰሜን እዝ ላይ ጭፍጨፋ በመክፈት ይፋዊ ጦርነት ከኢትዮጵያ ጋር የገጠመው ትሕነግ፣ በሦስት ሳምንት ውስጥ ተቀጥቅጦ የተጸነሰበት ጉድጓድ ቢገባም፤ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መቀሌን መልቀቁን ተከትሎ፣ እግር በእግር በጀመረው የጦር ወረራ እና ዘረፋ ገፍቶበታል። አሃዱ ብሎ ዘረፋውን የጀመረውም በዋግ አብርገሌ እንደሆነ ልብ ይሏል።
ከውስጥ ባሉ ባንዳዎች በመታገዝም፣ ዋግ ከተማን በተከታታይ ውጊያዎች እና የታቀዱ ውድመቶች ወደ ፍርስራሽ እየቀየራት ነው። በድህነትና በመሠረተ-ልማት እጦት ሲሰቃይ የነበረው ሕዝብ፣ ከ30 ዐመት በኋላም በዚሁ ከሀዲ ድርጅት ተጨፍጭፏል። ተፈጥሮ አስገደዳ ጎረቤቱ ባደረገችው የትግሬ ወራሪ እና አሸባሪ ድርጅት እየደማ ነው። ትላንት በመንግሥታዊ ድህነት አድቅቆ ሊገዛው ሞከረ፤ ዛሬ ደግሞ የጦር አውድማ አድርጎት በተደራጀ ዘረፋ እራቆተው።
Be the first to comment