
አዲስ አበባ ገና አልተነቃቃችም። በጎዳናዎቿ የሚታዩት በጠዋት ሥራ የሚገቡ ታታሪ እግረኞችና ለትራፊክ ሕግ ግዴለሾቹ ሚኒባስ ታክሲዎች ናቸው። በርግጥ “ሥራ ክቡር ነው” የሚሉ ቀማኞች ማልደው ተነስተዋል። ብጣሽ ጨርቅ ያነጠፉ የእኔ ቢጤዎችም አላፊ-አግዳሚውን ያዋክቡታል። “ስለእየሱስ ክርስቶስ…”፣ “አላሃ… ይስጥልኝ”፣ “አግኝቶ ከማጣት ይሰውራችሁ”… በጠዋቱ ከታክሲ ረዳቶች ቀጥሎ የሚሰማው ድምጽ ከርጥባን ጋር የተያያዘ ነው። ለውጡ፣ መንፈስ ይሁን መናፍስት ገና ያለየለት በመሆኑም፣ “ስለ ዶ/ር ዐቢይ…” የሚል ፎጋሪ አይጠፋም።
…በተመሳሳይ ሰዓት በሸገር መሃል በተንሰራፋው “ደንበል ህንፃ” ውስጥ፣ በሃያዎቹ መጨረሻ የሚገኝ መልከ መልካም ወጣት ወደ ላይኛው ፎቅ መጣደፉን ያስተዋለው የለም። ምናልባት ለእፍታ የተመለከተው ሰው ቢኖር፣ ፊቱ ላይ የተቸከቸከውን ታላቅ ተስፋ መቁረጥ አንብቦ፣ ሊቀ-መላአኩን በሆነለት ነበር። ብቻ አንድ፣ ሁለት፣ ሦስት… አስራ አንደኛ ፎቅ ደረሰ። ጥቂት ዘግይቶ፣ ዓይኖቹ ከሊፍቱ ውስጥ ተቻኩላ የምትወጣ እንስት ላይ አረፉ። አብዝቶ የሚወዳት ታላቅ እህቱ ናት። በጠዋት እንድትመጣ የደወለላት እሱ ነው።
አሁን የመጨረሻው ሰዓት እንደደረሰ አሰበ። ባዶ በሆነው የህንጻው የውስጥ ክፍል ቁልቁል ወደ ታች ተወረወረ። ሦስተኛው ፎቅ ላይ ሲያርፍ፣ ህይወቱም አብራ አለፈች።
ክቡራትና ክቡራን፡- ይህ አሳቃቂ ታሪክ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ረዳት አብራሪው ፍፁም እሸቱ ነው። ፍፁም ማን ነው? እዚህ ውሳኔ ላይስ ለምን ደረሰ? የሚሉትን ጥያቄዎች እያሰላሰላችሁ ተከተሉኝ።
(በነገራችን ላይ፣ መጽሔታችን የተቋሙን አስተዳደራዊ ጉዳዮች ለተመለከቱ መረጃዎች ትኩረት የምትሰጠው፣ ከአገሪቱ ወደብ አልባነት አኳያ፣ ከብሔራዊ ጥቅምና ደህንነት ጋር የተሳሰረ በመሆኑ ነው።)
በዚህ ተጠየቅም፣ ከባድ የሳይበር ጥቃት ስለመፈጸሙ፣ አውሮፕላን በአንድ ዶላር ስለመከራየቱ፣ ቁጥራቸው የበዛ ተጋሩ ሠራተኞች ስለመኮብለላቸው… በምርመራ ዘገባ የተጠናከሩትን ጨርፈን እናያለን።
የተድበሰበሰው የሳይበር ጥቃት
ዓለም ወደ ዲጂታል ተቀይሯል። ከቅያሪውም ጋር አነስተኛና ጥቃቅን ተቋማት ሳይቀሩ፣ አሠራራቸውን አዘምነዋል። ወረቀት ይዞ በየቢሮ መሽከርከሩ፣ “ደህና ሁን!” ከተባለ ሰንብቷል። ….
Be the first to comment