
ከመሬት ወረራ ወደ ማንነት ጥያቄ:
በዘመነ ትሕነግ፣ የኦሕዴድ ካድሬ አዲስ አበባ እና ዙርያው ላይ ያለውን መሬት በመቀራመት ፊት-አውራሪ እንደነበረ አይዘነጋም። ሁላችንም እንደምናስታወሰው፣ ድርጅቱ ላይ የተለጠፉ ካድሬዎች ከራሳቸው አልፈው ተርፈው፣ ለሌላው መሬት በማደልም ሆነ በመቸብቸቡ ረገድ የሚስተካከላቸው አልነበረም። በርግጥ፣ ይኽን የዐደባባይ እውነት እነሱም ክደውት አያውቁም። ከ8 ዐመት በፊት፣ በእነ አባዱላ ገመዳ መሬት የተሰጠው አንድ የምቀርበው ኦሮሞ ጉዳዩን ቀለል አድርጎ ያጫወተኝን አስታውሰዋለሁ። መምህራን ተሰብስበው አለን የሚሉትን ጥያቄ ያቀርባሉ። እነ አባዱላም መሬት እንደሚሰጧቸው ቃል ገብተው አፋቸውን ያስይዟቸዋል። በሌላ ጊዜ፣ የድርጅቱ ካድሬዎች እነዚያኑ መምህራን ሰብስበው፣ የተሰጣቸውን መሬት ምን እንዳደረጉት ሲጠይቋቸው፣ “ቤት እንዳንሠራበት ገንዘብ የለንም፤” የሚል አጭር ምላሽ ይሰጧቸዋል። በወቅቱ፣ ኦሕዴዶች ለዚህ ችግር መፍትሔ አድርገው ያቀረቡት ሌላ ተጨማሪ መሬት በመስጠት አንዱን ሸጠው፣ በሌላኛው ቤት እንዲሠሩ ነበር። ይህን ያደረጉት ለመምህራኑ አዝነው አይደለም። መሬቱ ከአርሶ ዐደሩ የተቀማ እንጂ፤ ከሰማይ የወረደ እንዳልሆነ ጠንቅቀው ያውቃሉ። በወቅቱ፣ የድርጅቱ አመራሮች ይህን እርምጃ የወሰዱበት ዋናው ምክንያት ከመምህራን የተነሳባቸውን ተቃውሞ አቀዝቅዘው፣ ለጊዜውም ቢሆን ድጋፍ ለማግኘት ነበር። የዘመኑ ተቃውሞ ማብረጃ መላ ይህ እንደነበረ በታሪክ እንዳይረሳ ሆኖ ተመዝግቧል።
እዚህ ጋ ልብ መባል ያለበት፣ ለመምህራን ሁለት ሁለት መሬት የሚያድል ካድሬ፤ ለራሱ ምን ያህል ሊቀራመት እንደሚችል መገመቱ ቀላል አለመሆኑን ነው። ሦስት? አራት? ዐሥር? ወይስ ከዚያ በላይ?
ዘግይቶ የመጣው የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጉዳይ ደግሞ ኦሕዴድ በግለሰብ፣ በማኀበራት… እየሸነሸነ ሲያከፋፍል የነበረውን አካባቢ የሚመለከት ነበር። እነሱ ግን ጥያቄውን ጠልፈው ለፖለቲካ የበላይነት መታገያ ወደማድረግ ለወጡት እንጂ። በዚህም፣ ራሳቸው በግላጭ ዋና አሳላፊ ሆነው የአርሶ ዐደር መሬት ያስወረሩበትን አጀንዳ ወደ ማንነት ጥያቄ ለመቀየር አልከበዳቸውም። ሙዝ እንደ መላጥ ቀሏቸው ነበር። ማስተር ፕላኑን ተከትሎ የተቀሰቀሰው ቁጣ፣ ‹ኹነቱ አዲስ አበባ ወደ ኦሮሚያ እንድትስፋፋ የሚያደርግ ነው› የሚል ይዘት አለው። የኦሮሚያ ካድሬዎች የወቅቱን አጋጣሚ ከላይ ሲታይ የማንነት እና የፍትሐዊነት ጥያቄ በማስመሰል ሲያቀርቡት፤ በውስጠ-ዘ ግን፣ ሕወሓት የፌደራል መንግሥቱ ላይ የነበረውን የበላይነት፣ በኦሕዴድ ለመተካት ወደሚያስችል ግብ ቀይረው አስጮኹት። በዚህም፣ ከአርሶ ዐደር የመሬት ነጠቃ ጥያቄ አልፈው፣ የአፍሪካ መዲና የሆነችውን አዲስ አበባን የሚጠቀልሉበትን ኃይል ማሰባሰቢያ አጀንዳ አደረጉት።
Be the first to comment