
የዓለም ምግብ ድርጅት ዛሬም ይነጫነጫል። “መኪኖቼ አፋር ላይ ተያዙ” ይላል። የአሜሪካ የጸጥታው ምክር ቤት ተወካዮች ዛሬም ”ያልተገደበ የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት ይመቻችልን፤ መስመር ይከፈትልን” ይላሉ። ራሺያ እና ቻይና ይቃወማሉ። ፕሬዚዳንቱ “የምሰጠውን እርዳታ ለጊዜው ነፍጌያለሁ” ይላሉ። ኢትዮጵያም በሰሜኑ በኩል ጦርነት ላይ ነች። ሕወሓትም “በምግብ እጥረት ሕዝቤን ሊፈጁ ነው፤ በሱዳን በኩል መውጪያ ኮሪደር ይሰጠኝ፤ ጦርነት የሚችለኝ የለም፤” ይላል። የአዲስ አበባው መንግሥትም “ወንበዴዎቹን አጠፋለሁ” ይላል። “ዓለም ዐቀፍ እርዳታ ድርጅቶች በስንዴ ፋንታ፣ ክላሺንኮቭ ሲያመላልሱ ይዘናቸዋል፤” ይላል ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር። እነ ቢቢሲም፣ እነ ቻነል ፎርም… የረሃብ፣ የመደፈር ዜናዎችን እና ዘጋቢ ፊልሞችን ያለመታከት ያቀርባሉ። ቢለኔ ስዩምም፣ እነ ዴክላን ዋልሽን ከአገር ታባርራለች…
ይሄ ሁሉ፣ በእርግጥም የዛሬ ሃቅ ነው። ጥቂት መለስ ብሎ ላስተዋለው ግን፣ የትላንትም ይሆናል። ትላንት፣ ከአርባና ሃምሳ ዐመታት በፊት፣ ተመሳሳይ ታሪኮች በአገራችን ተስተናግደዋል። በተመሳሳይ ግጭቶች እና ድራማዎች፣ ወዳጅ እና ጠላቶች፣ ተስፋ እና ስጋቶች ታጥራ ነበር። እነዚህን የቅርብ ጊዜ ሃቆች መለስ ብሎ ማየቱ፣ ለዛሬ የሚሆን ነገር አይጠፋውም። በዚህ መጣጥፌ ከታሪክ ሃቆቻችን ጋር ትንሽ እናወጋና፤ የነገ አካሄዶችን ለማስታወስ እሞክራለሁ።
“ከንጉሡ እስከ ደርጉ”
የንጉሡን መጨረሻ ክፉኛ ካጨለሙት ክስተቶች መካከል፣ የ1966ቱ የሰሜን ኢትዮጵያው ድርቅና ረሃብ ዋናው ነበር። የጆናታን ዲምበልቢ ዘጋቢ ፊልም በቢቢሲ ይፋ ሆነ። “ረሃብ የለም ሲሉ ነበር” በሚል ወቀሳ መተንፈሻ አጥተው የነበሩት ንጉሥም በመጨረሻ አመኑ ተባለ። “እርዱኝ” ሲሉም፣ የአገሪቱንም ሆነ የውጭ የሃማኖት ተቁዋማትን ተማጸኑ። Christian Relief and Development Association’ (CRDA) የተባለው ድርጅት የተመሰረተውም ለንጉሡ ጥያቄ ምላሽ ነበር። ከ20 ቤተ-እምነቶች የተወጣጡ ተወካዮች አንድ የጋራ ኔትዎርክ ዘረጉ። መካነ እየሱስ እና የካቶሊክ ሴክሬታሪያት ዋናዎቹ ነበሩ።Concem፣ SCF-UK እና Oxfam የተባሉ ድርጅቶችም “እናግዛችሁ፣ ልምድ ስላለን” ብለው ተቀላቀሉ። ማኀበሩ ”የልማተ ሥራዎችን የማስተባበር እና የማስፋፋት ዓላማ አለኝ፤” ይል ነበር።
Be the first to comment