
ዐድዋ፣ ኢትዮጵያውያን በምልዓት የተሳተፉበት፣ የዓለም ጥቁር ሕዝብ በምልዓት የተነቃቃበት የድል በዓል ነው። ኢሕአዴግ፣ በዐፄ ምንሊክ በቋጠረው ስር-ሰደድ ጥላቻ ዐድዋን ጥሎ፣ ግንቦት ሃያን አንጠልጥሎ ተወዛግቧል። ሕዝባዊውን ገድል ጨቁኖ፤ የብሔር ብሔረሰቦች ጭፍራን፣ ገዥ-መተርጓሚ አድርጎ ቆይቷል። ከ‹ለውጡ› በኋላ ደግሞ አክባሪው በዝቷል። ዘንደሮማ፣ ምርጫው ነው መሰለኝ፤ በምንሊክ ቤተ- መንግሥት፣ የ“ፒኮክ መንግሥት”ን የደረበው ብልፅግና፣ ‹ዐድዋ ወይም ሞት!› ባይ ሆኗል።
ኢትዮጵያ የዘመን ብዛት ያላደበዘዘውን ይህንን ድል ለመቀዳጀቷ፣ ውስጣዊ ጥንካሬዋ ጉልህ ድርሻ ነበረው። የማዕከላዊ መንግሥት መዳከም፣ ለእንግሊዞች መቅደላን የውሃ መንገድ እንዳደረገላቸው ሁሉ፤ የማዕከላዊ መንግሥት መጠናከር፣ ዐድዋን የጣሊያን መቃብር አድርጎታል።
በዚህ ዐውድ የምንሊክ መንግሥት እንዲጠነክርና ታሪክ እንዲሠራ ክቡድ አበርክቶ ያላውን ፖለቲከኛ እንዘክራለን።
ሰላም ላንተ! ራስ ዳርጌ ሣህለሥላሴ!!
እንዲህ እንደዛሬው የመንደር ጉልቤዎች በበዙበት “ዘመነ-መሳፍንት”፣ ንጉሥ ሣህለሥላሴ ሸዋን አንድ አድርገው፣ ሥርዐት ዘርግተዋል። አልፎ-አልፎ በጎሳ መሪዎች ከሚፈጠሩ ግጭቶች በቀርም፣ በተረጋጋው ግዛታቸው ሰላም አስፍነዋል። መቀመጫቻው አንኮበርም የአውሮፓውያን ዲፕሎማቶች፣ የአገር አሳሾች፣ የሚሽነሪዎች… መዳረሻ ሆና ነበር፤ (የአፍሪካ ቀንድ ታላላቅ ፖለቲካዊ ጉዳዮች የሚፈተትባትና ከታጁራ እስከ ዳህላክ ተጽእኖ የነበራትን ያችን አንኮበር እያስታወሱ፣ የዛሬዋን አንኮበር ማየት እንዴት ይረብሻል ጃል?!)
የጥላሁን ብርሃነ ሥላሴ “የ20ኛው ክፍል ዘመን ኢትዮጵያ” መጽሐፍ፣ ሣህለሥላሴ ከስምንት ሴቶች 15 ልጆች እንደወለዱ ይጠቅሳል። የበኩር ልጃቸው ከስልጤዋ ቁባታቸው ወ/ሮ ወሪጋ የተወለደው ዳርጌ ቢሆንም፤ ሥልጣናቸውን ያወረሱት ከሕግ ባለቤታቸው በዛብሽ ደጀን ለተገኘው ሁለተኛ ልጃቸው ኃይለመለኮት ነበር። …..
Be the first to comment