
የኢትዮጵያ ውስጣዊ ቅራኔዎች በተለየ የእድገት ምዕራፍ ላይ መገኘታቸው በግለጽ የሚታይ እውነታ ነው። ይህ ደግሞ፣ የድኀረ-83 ስጋቶች እና መዋቅራዊ ንቃቃቶች ስጋና ደም ለብሰው ወደ መጨረሻው ምዕራፍ እንዲጠጉ መግፍኤ ሆኗል። በዚህ ላይ፣ በብሔር አከላለል የተመተረችው አገር፣ “የዘር ማጥፋት” አጀንዳ የሚወሳበት ጦርነት ይዛ፣ የመፍትሔ አማራጮች ከጠረጴዛ ወደ ጠመንጃ ተሸጋግረዋል።
የሆነው ሆኖ፣ የኢትዮጵያን ውስጣዊ የቅራኔ ባሕርያት፣ የፖለቲካ ኃይሎች ግንኙነት እና የቅራኔዎች እድገትን በተመለከተ በሌላ ጊዜ የምመለስበት ሲሆን፤ በዚህ ዐውድ፣ አሁናዊው ውስጣዊ ቅራኔዎች ከውጪ ኃይሎች ተጽእኖ ነፃ ያለመሆኑን እንመለከታለን።
የኢትዮጵያ የቅራኔዎች ወቅታዊ ቁመና ከውጫዊው ተጽዕኖ በተጨማሪ፤ ፖለቲካዊ መፍትሔዎችን አልፎ፣ አንደኛ ዐመቱን የደፈነው ግጭት ውስጣዊ እና ቀጠናዊ ተጽዕኖ አለበት። ይህ ደግሞ፣ ድርብርብ ቅራኔዎች (multiple contradictions) የሚስተናገዱበት መድረክ እንዲሆን አስገድዶታል። ከቅራኔዎቹ መባባስም ሆነ መፈታት ጉዳይ ጋር በተያያዘ፣ በኢትዮጵያ አልያም በቀጠናው ጥቅማቸውና ፍላጎታቸው የሚነካባቸው ውጫዊ አካላት፣ ችግሮቹን በማባባሱም ሆነ በማቃለሉ ረገድ በተለያየ ሚና ከእነ ፍላጎቶቻቸው ተሳታፊ ሆነዋል።
የትኞቹ አገራት ምን ዐይነት ፍላጎት ይዘው፣ በአገራዊ ቅራኔዎቹ ውስጥ እንዴት እየተሳተፉ ነው? የሚለውን በመጠኑ እንመልከተው።
ሀ) የኤርትራ ፍላጎቶች እና የኢትዮጵያ ቅራኔዎች
የኤርትራ ነፃነት አንድም፣ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ፍላጎቶች ቅራኔዎች፤ ሁለትም የውጭ ኃይሎች ፍላጎቶች ቅራኔዎች ውጤት ነው። ትናንትም ሆነ ዛሬ፣ የኢትዮ- ኤርትራ ግንኙነት የእነዚህ ውስጣዊ እና ውጫዊ ፍላጎት- ወለድ ቅራኔዎች መስተጋብር እንደተጫነው ነው። ከዚህ አኳያም፣ በኢትዮጵያ ፖለቲካ፣ የኤርትራ ፍላጎቶች ምንድን ናቸው? የሚለውን ጉዳይ ማውሳቱ፣ ኤርትራ ዛሬም ሆነ ነገ በኢትዮጵያ ዙሪያ የምትጫወተውን ሚና መነሾ ለመረዳት ያግዛል። በኤርትራ በኩል፣ በኢትዮጵያ ካሉ የፖለቲካ ኃይሎች ውስጥ በዐደባባይ ከሚታየው ከትግራይ ልሒቅ ጋር ከገቡበት ቅራኔ በቀር፤ የተለየ ውግንና እና ባላንጣነት ሲራመድ አይታይም።
Be the first to comment