
ስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ከእነ ጉድለቱ ተካሂዷል። አሸናፊው ፓርቲ ብልፅግናም ምርጫው ነፃ፣ ፍትሐዊና ተአማኒ እንደነበር ለማሳመን ብዙ ርቀት ሄዷል። ከድህረ-ምርጫው ሰላማዊነት በቀር፤ ቅድመ-ምርጫው ከ97ቱ ጋር በምርጫ መስፍርቶች በፍፁም ሊነፃፀር አይችልም። ምርጫን እንደ መደበኛ ልምምድ ከመውሰድ ያለፈ ፋይዳ እንዳልነበረዉም ተገንዝበናል። ከሞላ ጎደል በአንድ ፓርቲ የበላይነት የተጠናቀቀው ምርጫ ዐዲስ መንግሥት ለመመስረት ተዘጋጅቷል። በርግጥ በነበረው እና ከነገ በስቲያ በሚመሰረተው ዐዲሱ መንግሥት መሃል የሚኖረው መሰረታዊ ልዩነት፣ «በምርጫ አሸንፌ የመጣው ነኝ» ከሚል ያለፈ የሚሆን አይመስለኝም። እንደ ዐዲስ የሚዋቀረው መንግሥት ካለፉት ሦስት ዐመታት የተለየ አስተሳሰብ ሊኖረው እንደማይችል ተገማች ነውና። ምናልባት አስተሳሰቡን ወደ መሬት ለማውረድ የሚሞክርበት ስልት ሊለወጥ ይችላል። እንዳለፉት ሦስት ዐመት፣ ዐዲስም ሊፈተን የሚችልባቸዉ መስመሮች ይኖራሉ። ከእነዚህ መስመሮች መካከል ጥቂቱን ለመዳሰስ እሞክራለሁ።
«ሕገ–መንግሥት»
የአንድ አገር ሕገ-መንግሥት ሲረቀቅ ሁሉም ዜጎች በተዋረድ የሚሳተፉበት ሊሆን እንደሚገባ ይታወቃል። በተቃራኒው የጥቂት ቡድንን ፍላጎትን ብቻ መሰረት አድርጎ ከተረቀቀ፣ እያደር የግጭት ምንጭ መሆኑ አይቀርም። አሁን ሥራ ላይ ያለው ሕገ- መንግሥት የሕወሓት የጫካ ሰነድ እንደሆነ ሰፊ ትችት ይቀርብበታል። አገርን ለብተና የሚያበረታታው ይህ ሰነድ ገና ከመነሻው የሕገ-መንግሥት አርቅቆት ሂደቶችን ባግባቡ ያላሟላ በመሆኑም፣ «የተፃፈበትን ቀለም ያህል ዋጋ የለውም» የሚል ትችት ሲሰነዘርበት ሰንብቷል። ሰነዱን ለማሻሻል አስቸጋሪ ሆኖ መዘጋጀቱ ደግሞ የዐዲሱ መንግሥት ቀዳሚው ፈተና ነው።
‹ሰነዱ አገርን ለብተና የሚዳርግ ሕገ-አራዊት በመሆኑ ተቀዶ መጣል አለበት› የሚሉ ኃይሎች፣ ወቅቱ አሁን እንደሆነ ያምናሉ። በሌላ በኩል፣ ፍፁምነቱን በመግለፅ ‹ሕገ-መንግሥቱ ከተነካ ኢትዮጵያ ትፈራርሳለች› የሚሉ ወገኖችም አሉ። ይህ ዐይነቱ መተናነቅ ዐዲሱን መንግሥት አጣብቂኝ ውስጥ መክተቱ አይቀርም። በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉት ጭምር ፈተናውን ሊያንሩት እንደሚችልም መገመቱ አያዳግትም።
Be the first to comment