
“ወደሽ ከተደፋሽ ቢረግጡሽ አይክፋሽ” ይላሉ አበው። ወዶና ፈቅዶ ወደ ጥፋት የገባን ሰው ልታድነው አትችልም። በአጉል ድፍረት፣ የዘንዶን ጉድጓድ በእጄ ካልለካው ያለህን “ተው ዘንዶ አለ …” በማለት ልታስጠነቅቀው ይገባል። “አልሰማህም! ምን አገባህ!?” የሚል ምላሽ ከሰጠኽ ግን ልትረዳው ማሰብህን አልፈለገም ማለት ነው። በሐዘኔታ ከንፈርህን ከመምጠጥ ውጭ ከቶም እጁን ከማጣት ልታድነው አትችልም። የዚህን እውነት ማጠናከሪያ አንድ ተረት ልጨምርለህ። እንሆ!
“የፍርደ ገምድል አገር”
አንዱ ነው አሉ። ከእጅ ወደአፍ የሆነውን ኑሮውን በመጥላቱ ምሬት ገባው። ለዘመናት የኖረበትን አካባቢ ትቶ ለመሰደድም ወሰነ። ‘ተው አንድ ቀን ያልፍልናል። አገርህን ለቀህ የትም አትሄድ። የዛሬን ሳይሆን የነገን ተስፋና እድል ተመልከት’ እያለ ጎረቤትና ዘመድ አዝማድ ቢለምነው አሻፈረኝ አለ። በወሬ ወደሰማው፣ ሀብት ወደተትረፈረበት አቅጣጫ፣ ቅልና ጨርቁን ጥሎ፣ ሚስቱንና ልጆቹን አንጠልጥሎ ጉዞ ጀመረ። ቀንና ሌት ተጉዞም የሁለት አገራት አካፋይ ድንበር ላይ ደረሰ። መንገዱ መስቀለኛ ነበር። ያ የሰማው የጥጋብ አገር የቱ እንደሆነ ለማወቅ ግን ቸገረው። ድንበሩ ላይ ሰዎች አገኘና ጠየቀ ።
በቀኝ አቅጣጫ ያለው ፍትህ፣ ርትዕና የሰው እኩልነት የሰፈነበት፣ ዳኞች ያለአድልዖ ለሁሉም ትክክለኛ ፍትህ የሚሰጡበት፣ ሁሉም በችሎታው ሰርቶ የመኖር መብቱ የተረጋገጠበት፣ የተሻለ ኑሮ ለማግኘት ግን እጅግ ልፋት የሚጠይቅበት አገር ነው። በስተግራው አቅጣጫ ያለው አገር ደግሞ፣ በፍርደ ገምድልነት የታወቁ ዳኞች የበዙበት፣ ህግና ሥርዓት የማይከበርበት፣ ምን ገዴ መንግስት ያለበት፣ ምግብና መጠጥ የተትረፈረፈበት እንዲሁም ዜጋው ማጭበርበርን ስራው አድርጎ በሌላ ሰው ድካም እንዳሻው እንዲሆን ህጋዊ ከለላ የተሰጠበት አገር ነበር። ይህንን እውነት ስደተኛው ሰው ተረዳ። እናም “ከርሃብ ይልቅ ጥጋብ ይሻላል። ህግ ከሚከበርበትና ችጋር ከሞላበት አገር ያለህግ በመኖር ሰማይን በእርግጫ መምታት የተሻለ ነው” በማለት የጥጋብና የፍርደ ገምድል አገርን መረጠ ።
ምንገዴ፣ ጥጋበኛና ፍርደ ገምድልነት በሞላበት አገር እንዳሻው እየበላና እየጠጣ ሀብት አፍርቶ፣ ተጨማሪ ሁለት ልጆች ወልዶ በተድላ ኑሮውን ቀጠለ። በአንድ ወቅት፣ ከአጠገቡ ጎጆ ቀልሶ የሚኖር የአገሬው ተወላጅ ልጅ ስለሌለው ቀናበትና “ሚሥትህን ሥጠኝ” ሲል ጠየቀው። ይኽ ጥያቄ ለአገሬው እንግዳና ያልተገባ አልነበረም። ይኽንን ጥያቄ ለማስተናገድ ፍቃደኛ ሳይሆን ቀረና ተከሶ ፍርድ ቤት ቀረበ።
Be the first to comment