
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰሞኑን ባካሄደው 6ኛ ዐመት የሥራ ዘመን 13ኛ መደበኛ ስብሰባ፣ ‹ሕወሓት› እና ‹ሸኔ›ን በሽብርተኝነት እንዲሰየሙ፤ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ያቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ አጽድቋል። ከጀርባቸው የፖለቲካ አስተሳሰብን ያነገቡት እነዚህ የሽብር ቡድኖች፤ እንቅስቃሴያቸው የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የወጣውን ዐዋጅ ቁጥር 1176/2012 አንቀጽ ሦስት ሥር፣ ስለ ሽብር ወንጀል ድርጊት የተሰጠውን ሙሉ ትርጓሜውን ሙሉ በሙሉ የሚያሟላ ድርጊት እንደፈፀሙ ታውቋል። የሕዝብ እንደራሴዎችም፣ ‹ውሳኔው ቢዘገየም ተገቢና ትክክለኛ› ሲሉ ድጋፋቸውን አሰምተዋል።
በአሸባሪነት የተፈረጁት ‹ሕወሓት እና ሸኔ› በተናጠልም ሆነ በጥምረት ኢትዮጵያ እንዳትረጋጋ ብዙ መስራታቸው ይታወቃል። ጥምረታቸው ከአገር ውስጥ ባለሥልጣናት እስከ ውጭ ኃይሎች መዘርጋቱ ኢትዮጵያን በእጅጉ ፈትኗታል። አገር የማተራመስ ዓላማቸውን ግብ ለመምታት፣ እንደ ዋና አማራጭ የወሰዱት ደግሞ በዐማራ ተወላጆች ላይ ያነጣጠረ ጭፍጨፋ መፈፀምን ነው። ከቅርቡ እንኳን ብንነሳ፡-
በማይካድራ፣ በመተከል፣ በአጣዬና አካባቢው፣ በወለጋ እና ሌሎችም የአገሪቱ ክፍሎች ውስጥ የዐማራ ተወላጆች ላይ የተፈፀመው ጥቃት በዓለም ላይ ከተፈፀመው የሽብር ሞት ቢበልጥ እንጂ የሚያንስ አለመሆኑን መታዘብ ተችሏል። በማንነት ላይ ያተኮረው ጭፍጨፋ፣ ማፈናቀል፣ ንብረት የመዝረፍና የማውደም ሁኔታ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ሕይወታቸው አልፎ፤ በመቶ ሺዎች የሚገመቱት ደግሞ ይኖሩበት ከነበረው አካባቢ ተፈናቅለዋል።
Be the first to comment