
በዘንድሮው ሀገር አቀፍ ምርጫ የሚሳተፉ የፖለቲካ ፓርቲዎች በምርጫው የተሻለ ውጤት ለማግኘት ውህደት ወይም ግምባር ፈጥረው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ። ከነዚህም መካከል ከወራት በፊት አብረው ለመስራት የተስማሙት ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) እና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የፈጠሩት ጥምረት ተጠቃሽ ነው። ፓርቲዎቹ በተለይም በአዲስ አበባ ጉዳይ የምርጫ ድምፅ እንዳይከፋፈል ለማድረግ እና በቅስቀሳ ወቅት ተባብረው ለመስራት ጥምረት መፍጠራቸው ይታወሳል።
ከሰሞኑ ደግሞ የአፋር ህዝብ ፓርቲ (አህፓ) እና ነፃነት እና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ጥምረት ፈጥረዋል። ፓርቲዎቹ አብረው ለመስራት የተስማሙት የምርጫው መጨረሻ ውጤት እስኪገለፅ ሲሆን፤ ምናልባትም በቀጣይ በሚደረጉ ስምምነቶች ጥምረቱ ሊቀጥል የሚችልበት እድል እንዳለ ተነግሯል። የነፃነት እና እኩልነት ፓርቲ ከዚህ ቀደም በሶማሌ እና ጋምቤላ ክልል ከሚወዳደሩ ፓርቲዎች ጋር አብሮ የመስራት ስምምነት ማድረጉ የሚታወስ ነው። የአሁኑም ጥምረት የዚሁ አካል እንደሆነ ፓርቲው አስታውቋል።
ስምምነቱ፣ መራጩ ህዝብ በተወዳዳሪ ፓርቲዎች ብዛት የሚያጋጥመውን መደነጋገር የሚያስቀርና በጋራ የመስራትን ጠቀሜታ የሚያሳይ እንደሆነ ፓርቲዎቹ ተናግረዋል። የስምምነት ፊርማው ‹‹ፓርቲዎቹ የፖለቲካ መስመራቸውን ወደ ህዝብ የሚያሰርጹበት፣ ከተፎካካሪነት ወደ አሸናፊነት የሚያሸጋግራቸውን እድል የሚፈጥሩበት እንደሆነ›› የአፋር ህዝብ ፓርቲ (አህፓ) ሊቀ መንበር አቶ ሙሳ አደም ገልጸዋል። ፓርቲዎች በስድስተኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ በአፋር ክልል ምክር ቤት እና በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተወዳድረው ውጤታማ መሆን እንደሚያስቸላቸው እምነት አሳድረዋል።
Be the first to comment