
ከ1966ቱ የኢትዮጵያ አብዮት በኋላ ለተራዛሚ ዐመታት በሰሜን ኢትዮጵያ የተካሔደው ጦርነት በዋግኽምራ ዞንም የተፈጥሮ ሃብት መመናመንን በማስከተል የአፈር ለምነቱ የተራቆተና አምራችነቱ በየጊዜው እየቀነሰ የተመናመነ አካባቢ አድርጎታል። ልጆቹን ገብሮ የደርግ አምባገነን መንግሥት የተፋለመው የዋግኸምራ ሕዝብ፣ የድሉ ውርስ የትግራዩ ትሕነግ ተስፋውን ነጥቆ ለሦስት ዐሥርታት ለዘለቀበት የአምባገነንነትና ምዝበራ ሥልጣን ማብቃት ነው የሆነው።
ከዘመናት የጦርነት አዙሪት በኋላ ድል ያገኘው የዋግ ሕዝብ፣ በተለይ ከድኀረ-83 ትልቅ የመልማት ተስፋ ነበረው። ነገር ግን በወያኔ ሙሉ ቁጥጥር ስር የወደቀው መንግሥት አራት ኪሎ እንደደረሰ በዋግ ሕዝብ ላይ ክሕደቱን ጀመረ። የክህደቱ መጀመሪያ የድል ሽሚያ ውስጥ ገብቶ የዋግ ሕዝብ በ17 ዐመታት ጦርነት የከፈለውን ዋጋ እና ለጦርነቱ ያደረገውን ድጋፍ ማቃለል ነው። “የኢሕዴን ሚና ከወታደራዊ ይልቅ፣ ፖለቲካዊ ነው” በማለት የዋግ፣ የጎንደር በለሳ እና ወሎ ታጋዮች ትግልና መስዋዕትነትን፣ ትሕነግን አራት ኪሎ የማድረስ ፖለቲካ አድርጎት አረፈ።
የጦርነት ወታደራዊ ሚና በሟችና ቁስለኛ ብዛት የሚወሰን በማስመሰል፣ የዋግ ሕዝብ ከሌለው ሃብት ላይ ስንቅ እያወጣ፣ የ1977 ድርቅና ረሃብ መከራ እየወረደበት፤ እንዲሁም የደርግ መንግሥትን የአውሮፕላን ድብደባ ችሎ፣ ከ6 ሺሕ በላይ ልጆቹን ገብሮ የመጣን ድል የራሱ ብቻ አስመስሎ ሰብኮታል።
በመቀጠልም ትሕነግ በዘመኑ የነበረውን የኃይል ሚዛን ብልጫ በመጠቀም በዐማራ ክልል ሕዝብ ላይ ባደረሳቸው የማንነትና ግዛት አንድነት ጥቃቶች የዋግሕምራ ሕዝብ የጥቃቱ ሰለባ ነው። “አገር ማለት ሕዝብ ነው” እያለ ግዛት ጥቅለላን ሲያሰላና ሲፈፅም፣ ለሕዝብ ማንነት ቆሜያለሁ እያለ የማንነት ጥያቄን ሲደፈጠጥ የኖረ ጠላት ነው። እናም የሽግግር መንግሥቱን ማክተም ተከትሎ፣ በ1987 ዓም ትሕነግ ክልሎችን ከራሱ መጻኢ ጥቅም ጋር አስልቶ አካልሏል። በዚህ የአከላለል ሂደት የዋግ ሕዝብ በሦስቱም አቅጣጫ እንዲሸራረፍ ከመደረጉ በላይ፤ በየጊዜው ብዙ መሬቶች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸው እየተሳላ በጉልበት ተነጥቀው ወደ ትግራይ ተካልለዋል።
Be the first to comment