
በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መጋቢት 2 ቀን 2013 ዓ.ም መግለጫ የሰጠው ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ፣ እየተከናወኑ ያሉት ሀገራዊ ችግሮችን ‹‹መንግስታዊ ሽፋን የተሰጠው የዘር ማጥፋት ወንጀል›› ሲል ይከሳል። የድርጅቱ አባላት ላይ የተላለፈውን ውሳኔ ደግሞ ‹‹የምርጫ ቦርድ አሻጥር›› ሲል ገለልተኝነቱን አጠይቋል።
መግለጫው ቅድሚያ የሰጠው ምዕራብ ኦሮምያ ክልል፣ ወለጋ- ሆሮጉድሩ ወረዳ ውስጥ ከየካቲት 27 ቀን 2013 ዓ/ም ጀምሮ በተፈጸመ ጥቃት ‹‹ከ60 በላይ ንጹሃን ዜጎች ህልፈት>> የተሰማውን ጥልቅ ኃዘን በመግለጽ ነው። ለችግሩም ‹‹በኦህዴድ/ብልጽግና ይሁንታና በኦነግ ሸኔ አድራጊነት›› ተከናወነ የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው ብሎ እንደሚያምን ገልጿል።
እንደፓርቲው እምነት በአማራ ተወላጆችና በሌሎች ንጹሃን ዜጎች የሚፈጸመው ‹‹የዘር ማጥፋት ወንጀል›› ዋነኛው ተጠያቂ፣ ኦነግን ከኤርትራ በረሃ ወደ አገር ቤት ከነትጥቁ እንዲገባና በኦሮምያ ክልል ጸጥታ መዋቅር ውስጥ ኃላፊነት በጎደለው ሁኔታ እንዲካተት ያደረገው መንግስት እንደሆነ አስታውቋል።
ይሄንን አረመኔያዊ ድርጊት የፈጸሙና ያስፈጸሙትን ባልደራስ እንደሚታገልና ለህግ እንደሚያቀርባቸውም አረጋግጧል። በኦሮምያ ክልል የተለያዩ ዞኖች ለባለፉት 3 ዓመታት የቀጠለው የዜጎች ሞትና ማፈናቀል፣ ክልሉን እየመራ ያለው ‹‹ኦህዴድ/ብልጽግና፣ በተረኝነት አገርን ከመዝረፍ ውጪ መምራት እንደማይችል›› ማሳያ እንደሆንም መግለጫው ያትታል። በስልጣን ላይ ያለው ድርጅት በዚሁ ከቀጠለ ሀገሪቱን ለበለጠ ችግር ስለሚዳርጋት በመጪው ምርጫ ‹‹በቃህ ሊባል ይገባል›› ሲል መፍትሔ ያለውን ሀሳብ አቅርቧል።
ዜጎች በዚህ አይነት ሁኔታ ላይ በሚገኙበት ወቅት የሚደረግ ምርጫም ተአማኒነቱ አጠራጣሪ ይሆናል። በተጨማሪ መንግስት እንዲህ አይነቱ ዳተኝነት የሚያሳየው ‹‹በሥልጣን ለመቀጠል ካለው የሥልጣን ጥመኝነት ነው›› ሲል ፓርቲው እምነቱን አስቀምጧል።
1 Trackback / Pingback