
ከ2010ሩ ለውጥ በኋላ የ“አማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄን (አዴሕንን)” ጨምሮ፣ በትጥቅ ትግል ላይ የነበራችሁ ድርጅቶች፣ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ወደ አገር ቤት መግባታችሁ ይታወቃል። ይሁንና፣ ኦነግ ከሌሎቻችሁ በተለየ መልኩ ሠራዊቱን ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ሳያስፈታ መቆየቱ አነጋጋሪ ነበር። ይህንን ጉዳይ ድርጅታችሁ እንዴት ይመለከተዋል?
ከኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣ፣ ከመንግሥት ጋር በርካታ ስምምነቶችን አድርገናል። ነገር ግን መንግሥት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ስምምነቶችን ጥሶ፣ ድርጅታችንን በኃይል አፍኖ ለማፍረስ በጠነሰሰው ሴራ ከበረሃ ያመጣነውን ንብረቶቻችንን ሳይቀር፣ ሲዘርፍ ቆይቷል። ከዚህ ሁሉ በኋላ አፈር ልሰን ተነስተን ነው፣ ድርጅታችንን እንደገና ያቋቋምነው። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስመዝግበን እውቅና ካገኘ በኋላ በሰላማዊ መንገድ እየተንቀሳቀስን ነው። በእኛ በኩል ወደ ሰላማዊ ትግል የገባነው ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ፈተን ነው።
በሌላ በኩል፣ የኢትዮጵያ ፖለቲካ በአሻጥር የተሞላ በመሆኑ፣ ከእኛ ጋር እኩል የነበሩ ኃይሎች ታጥቀው፣ ከዛም በኋላ የተለያየ ስያሜ እየተሰጣቸው በርካታ ግፍና መከራ በሕዝባችን ላይ ሲያደርሱ ቆይተዋል።
ወደ አገር ቤት ከገባችሁ በኋላ፣ በቀድሞ አዴፓ ፓርቲ ችግር እንደተፈፀመባችሁ ስትናገሩ ነበር። ጉዳዩም ፍርድ ቤት እንደደረሰ ይታወቃል። አሁን እልባት አግኝቷል?
ከመንግሥት ኃላፊዎች ጋር በተለያዩ መድረኮች ተነጋግረን ያለፈው አዴፓ በእኛ ላይ የሠራው ስህተት እንደሆነ በተወሰደ ደረጃ መግባባት ላይ ደርሰን ነበር። ነገር ግን ገዢው ፓርቲም ሆነ መንግሥት ከስምምነት ላይ ከደረስንባቸው ነገሮች አንዱንም አልፈፀሙም። ለመፈፀምም ፍቃደኛ አይደሉም።
በፓርቲያችሁ አባላት መካከል አለመግባባቶች ይፈጠራሉ። አባላቶቻቸውም ድርጅቱን ለቀው ሲወጡ ይሰማል። ምክንያቱ ምንድን ነው?
Be the first to comment